ሊበሏት ያሰቧትን አሞራ ይሏታል ጅግራ – ፊልጶስ

”6ተኛውን ሀገራዊ ምርጫ ለማደናቀፍ በህቡዕ ተደራጅተው ሲንቀሳቀሱ የነበሩ ቡድኖችን እኩይ ሴራ ማክሸፉን የደህንነትና ፀጥታ የጋራ ግብረ ኃይል አስታወቀ።” ይላል የትላንቱ መግለጫ። ይህ መግለጫ ደግሞ በየድህረ-ገጾችና በማህበራዊ ሚዲያ ሲዘዋወር ውሏል። ያከሸፈው ከኢትዮጵያ ውጭ የሚገኙ ኢትዮጵያዊን (ዳያስፖራዎች ) በህቡ ሲንቀሳቀሱ ” አከሸፍኩ” ይላል መግለጫው።
የደህንነት መስራቤቱ እንደ እጣዩ ያለ ከተማ ሲወደም፣ በየቀኑ ህዝብ ከአፍንጫው ስር ሲታረድና ሲዘለዘል አይሰማማ! አያይም! ግን ባህር ማዶ የተጠነሰሰውን ሴራ አሽትቶ፣ በመነጸሩ አይቶ፣ አየር ላይ አከሸፈው። መቸም ”የጉድ አገር ገንፋ እያደር ይፋጃል ” ማለት ከዚህ ላይ ነው።

ደህንነት ደረስኩባቸው ያለው…. የማህበራዊ ሚዲያ ቡድኖች ለሁሉም ክፍት መሆናቸው ብቻ ሳይሆን፣ በባህር ማዶ ያሉ አምባሳደሮችና የራሱ የመንግስት ደጋፊዎቹ ሁሉ ያሉበት መሆኑ ገሃዳ ነው። ታዲያ የማህበራዊ ሚዲያ ቡድኖች “የብዛት ቁጥር” እየተጠቀሰ ጀብድ እንደሰራ ሁሉ በመንግስት ደረጃ ከወያኔ የተረከበውን ድራማ በእጥፍ አሳድጎ መግለጫ ሲያወጣ ” ወይ አገሬ ፣ ማን ላይ ነው የወደቅሽው ? ” ያሰኛል። እንዴት በህቡ የሚንቀሳሰቀስ አነድ አካል /ድርጅት የማህበራዊ ሚዲያ ቡድኖች ሆነ ስራውን ለሁሉም ዜጋ ክፍት ያደርጋል? ” ነገሩ ”ሊበሏት ያሰቧትን አሞራ ጅግራ ይሏታል።” ነው።
ለዚህ ደግሞ መግለጫው እንዲህ ይላል፤
“ደህንነትና ፀጥታ የጋራ ግብረ ኃይል በመግለጫው፤እነዚህ ሃይሎች ለጥፋት እቅዳቸው ተፈጻሚነት ከአንድ አንድ ተፎካካሪና የገዢው ፓርቲ አባላትና አመራሮች እንዲሁም በስራ ላይ ካሉና ከለቀቁ የጸጥታና ደህንነት ተቋማት አባላት ጋር በመቀናጀት በህቡዕ ከተደራጁ ታጣቂ ቡድኖች ጋር ትስስር ፈጥረው ሀገራዊ ትርምሱን ለመምራት እቅድ አውጥተው ሲሰሩ መቆየታቸውን የግብረሃይሉ መግለጫ አብራርቷል።”
እውነታው አገር ቤት ውስጥ ያሉትን የገዥውን አካሄድ ያልተቀበሉና በምርጫው ብልጽግናን ሊያቸንፋ በሚችሉ የፓለቲካ ፓርቲዎች ላይ ከዲያስፓራ ጋር ንክኪ አላችሁ ብሎ ለማስወገድ ወይም ለማሰር ወይም ሽብርተኛ ለማለት የታለመ አሳፋሪ፣ አሳዛኝና ገዥው መያዥና መጨበጫ ያጣበት መገልጫ ነው። በዚህ መግለጫ ደግሞ ለመምታት የታሰበው በተለይም ባልደራስን እና አብን መሆኑ ግልጽና ገሃድ ነው።

” በውኔም አየኋት፣ ኢትዮጵያን እማማ’
በህልሜም አየኋት ፣ አገሪን እማማ
በ’ሾኽ በታጠረ መንታ መንገድ ቁማ።

በጣም አሳፋሪውና ስለ ኢንተርፖል ማንነት የሰናፍጭ ያህል እንኳን መንግስት የሚያክል አገርን የተረከበ ኃይል ምንም ግንዛቤ እንደሌለው የሚያሳየው የሚከተለው ነው፤
” …..በወዳጅ ሀገራት ትብበርና ከኢንተርፖል ጋር በመቀናጅት በቁጥጥር ሥር ውለው በህግ ተጠያቂ ለማድረግ እየተሰራ መሆኑን የጋራ ግብረሃይሉ ባወጣው መግለጫ አረጋግጧል።”
የደህንነት መስራ ቤት ሆይ!.. ኢንተርፖል አ’ተን ራስክን በአሸባሪነት እንደሚከስህ አልሰማህምን? አንተ አትሰማም! የምትሰማው መስማት የምትፈልገውን ብቻ ነውና።
መንግስት ሰላሳ ግዜ ”ምርጫ! ምርጫ!” ከማለትና የፈጠራ ድራማ ከመሰራት ይልቅ በየቀኑ በራሱ የመንግስት መዋቅር ተዘርግቶ የሚገደሉ ዜጎችን ደህንነትና ህልውና ቢጠብቅ ከእንዲህ ያለ አጣብቂኝ ውስጥ ባልገባ ነበር። ባዕዳን ኢትዮጵያን ለመሰልቀጥ እንዲህ በቋመጡበትና ግዜው ዛሬ ነው ባሉበት ሰዓት ህዝብን እሰተባብሮ በአንድነት እንዲቆምና አገርን እንዲታደግ በማደረግ ፋንታ፣ ስለ ኢትዮጵያና ኢትዮጵያዊነታቸው መሰዋአት ሲከፍሉ የኖሩትን፣ አሁንም ለአገራቸው እንድነትና ክብር ከሆነ አንገታቸውን ከመስጠት ወደ ኋላ የማይሉትን ዜጎች በፈጠራ ክስ መወንጀል የሚጎዳው ህዝብናን አገርን እንጅ ማንንም አይደለም። “የነብር ጅራት “ የሆነባችሁ ስልጣናችሁም ይከዳችኋል።

ምርጫውን በተመለከት እኔና የኔ ብጢዎች የምንቃዎመው ምዕራቡ ዓለም ስለተቃዎመ ሳይሆን፣ ገና ከጅምሩ ምርጫ ይደረጋል ሲባል፣ “ለአንድ መንግስት የሚቀደመው የዜጎችን ድህንነትና የአገሪቱን ልዋአላዊነት ማሰጠበቅ ነው፡ ምርጫ አሁን ለኢትዮጵያ ህዝብ ቅንጦት ነው፣ አገራችን በመንግስት ስር በተሰገሰጉ ባንዳዎችና በውጭ ኃይሎች እንደ ገና ዳቦ እየነደደች ነው፡ ።” ከሚል ፍጹም ኢትዮጵያዊነት ፍቅር እንጅ ሌላ እለነበረም።”
አሁንም መንግስት በፍርሃት ቆፈን ተይዞና በራስ መተማመንን በማጣት የገዛ ዜጋን በውሸት በመወንጀል ትርፍ አገርን ለውድቀት የሚዳርግ በመሆኑ ቆም ብሎ ሊያስብ ይገበዋል።
የህዳሴውን ግድብ በተመለከተ ከራሱ ከመንግስት ባንዳዎች ውጭ፣ መንግስት አሁን በያዘው አቋም እንዲቀጥልና እንደ ዜጋ መላው የኢትዮጵያ ህዝብ የሚጠበቅበትን ሁሉ እይደረግና ለማድረግም ዝግጁ መሆኑን መገንዘብና ምርጫው አሁን ግዜው አይደለም የሚሉትን ለአገርና ለወገን አስበው እስከሆነ ድረስ በሰከነ መንፈስ ጆሮ ሰቶ ማዳመጥ ብልህነት ብቻ ሳይሆን ‘መንበሩን ስለያዝኩ እኔ ብቻ አውቃለሁ’ ለወያኔም እንዳልበጀው ማወቅ መልካም ነው። መንግስት ህጋዊ ሆነ አልሆነ (ኢህዲግ ሲፈርስ ህጋዊነቱ አክትሟል) የኢትዮጵያ ህዝብ ቅድሚያ የሚፈልገው በሰላም ወ’ቶ መግባትና የአገሩ ልዋአላዊነት መሆኑ መዝንጋት የለበትም። ህዳሴ ግድቡም የዚሁ አካል ነው።
እናም መንግስት የደህንነት ክፍሉ ያወጣውን መግለጫ ከአሁን በኋላ ”ውሾን የጠራ ውሾ” ቢያደገው ለአገር፣ ለወገንም፣ ለራሱ ለገዥውም ይጠቅማል፤ በአንጻሩ ባንዳዎችን እና በዕዳን ጠላቶቻችንን በጋራ ለመመከት ያስችለናል።

ኢትዮጵያ ለዘላለም ትኖራለች!!
——-//—-ፊልጵስ

About expeder

Check Also

ከኢትዮጵያዉያን ማህበር በአዉሮፓ የተሰጠ ጋዜጣዊ መግለጫ

PressRelease-AMHARIC- by A.E.E-March 23-2024

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *

99 − = 96